2014 ማርች 10, ሰኞ

ጉድ በል ጎንደር- ‹የመለስ ካምፓስ› በጎንደር ዩንቨርሲቲ!!

አስታውሳለሁ በ1999 ዓ.ም. የጎንደር ዩንቨርሲቲ አንደኛው ካምፓስ ስም ይሰጠው ተባለ እና ተማሪው ሁሉ ተወራከበ፡፡ ከማራኪ ካምፓስ በታች በኩል ያለው ካምፓስ ስያሜ ብዙ አጨቃጨቀ፡፡ ከዚያም ተማሪዎች ፊርማ አሰባሰቡ- አጤ ቴዎድሮስ ካምፓስ ይባል ተባለ፡፡ ከዩንቨርሲቲው አመራሮቸች ጋ ‹‹የነፍጠኛ ስም›› ነው የሚል ቅራኔ ቢኖርም በጊዜው ከነበረው የፖለቲካ ትኩሳት አንጻር ያን ስያሜ መቃወም ማለት አላስፈላጊ ብጥብጥ መፍጠር ነበር - እናም ስያሜው ጸደቀ፡፡ የከተማ ታክሲዎች አንዳች አገራዊ ፋይዳ ያለው አዋጅ እንደታወጀ በመቁጥር ‹‹አጼ ቴዎድሮስ ካምፓስ›› የሚል ወረቀት ጽፈው በጣም አስተዋወቁት፡፡ ከዚያ በኋላ ጎንደር ተረት የሆኑ ነገስታቶቿን ለማስታዎስ ይመስላል አሁንም ሌላኛውን ካምፓስ ‹‹ፋሲል›› ካምፓስ ተባለ፡፡ ከአመታት በኋላ ደግሞ ከከተማው ወጣ ብሎ ሌላ ካምፓስ ተገነባ፡፡ ይህ ካምፓስ ከከተማው ትንሽ ወጣ ያለ በመሆኑ ከተማሪ ትክተት ውጭ ነው፡፡ የዚህን ካምፓስ ስያሜ ለማውጣት ግን ተሜን ማማከር እንደቀድሞ አስፈላጊ አልነበረም፡፡ ከዩንቨርሲቲው ሴኔት ይሁን ከፌደሬሽን ምክር ቤት በተላለፈ ውሳኔ ‹‹መለስ ካምፓስ›› ተባለና በቅርቡ ተመረቀ፡፡ ግልጽ መሆን የነበረበት ለምን መለስ መባል እንዳስፈለገው ነው፡፡ መለስ በየሀገሩ ሁሉ ብዙ ቦታ ተሰይሞለታል፡፡ ‹መለስ ፓርክ፣ መለስ ሆስፒታል፣ መለስ ትምህርት ቤት፣ መለስ ጤና ጣቢያ፣ መለስ....› ብዙ መለስ የሚባሉ ቦታዎች ከከጋምቤላ እስከ ቶጎጫሌ፣ ከዛላንበሳ እስከ ሞያሌ ድረስ አሉ፡፡ በሁሉም አቅጣጫ ቢያንስ በአማካይ 10-20 ኪሌ ሜትር ርቀት ያለማጋነን በመለስ ስም የተሰየመ ነገር አይታጣም፡፡ በአማካይ 10-20 ጫማ ርቀት ደግሞ ስለ መለስ ራዕይ የሚሰብክ ሰው አይታጣም፡፡ ይህ ሆኖ ሳለ ስለምን ዩንቨርሲቲውን መለስ አሉት ቢባል መለሱ ግራ ያጋባል፡፡ ምናልባትም ‹መለስ የተማረ ሰው ስለሚወዱ› የሚል ካለ ተሳስቷል፡፡ ምክንያቱም በመጀመሪያ ከደደቢት በረሃ አራት ኪሎ ሲደርሱ አቶ መለስ ያደረጉት ነገር ቢኖር 44 በላይ ‹‹አሉ የተባሉትን›› የሀገሪቱን ምሁራንና ተመራማሪዎች ነው ድራሽ ያጠፋቸው፡፡ (በዚህ ሰዓት ከአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ የተባረሩ ሰዎችን ዝርዝር እያየሁ ነው ያሰብኩት፡፡) ተያይዞም የጎንደር ዩንቨርሲቲ ምክትል ፕሬዚዳንት መለስ ከሞቱ ቀደም ብሎ በመኪና አደጋ ህይወቱ ሲያልፍ ሌላው ለጎንደር ህዝብ አጠያያቂ አሟሟት ነበር፡፡ ምናልባትም አሁን በጎንደር አንድ ካምፓስ የተጀመረው ስያሜ አዲስ አበባ ባሉት ሁለት ዩንቨርሲቲዎችም አንደኛውን ሙሉ በሙሉ ዩንቨርሲቲው ‹‹መለስ ዩንቨርሲቲ›› ሊባል እንደሚችል ከወዲሁ መገመት አያዳግትም፡፡

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ