2014 ማርች 11, ማክሰኞ

ግብረ ገብነት ሆይ ማደርያህ ከወዴት ነው? ክፍል ሁለት

ካንገት በላይ ስንስቅበት - የዘመኑ ጥርስ አረጀ፤ ሳቅ ራሱ ጥርስ ናፈቀ - ጥርስም ፈገግታን ጎመጀ፤ ምነው ሰው ሁሉ ሳቅ ራበው! ምነው ሰው ሁሉ ጥርስ አጣ! ቁም ነገር ዳዋ ለበሰ - ህይወት ሆነ የለበጣ! ጥርስ መሳቂያ ጊዜ አጣ - ማኘክ ብቻ ሆነ ስራው! ከልክ በላይ መብላት ለምዶ - ሆዳችን እያስፈራራው! የትውልድ ጥርስ ሻገተ - አጓጉል ስራ በዛበት! ያልሰራንበትን ጎርሰን - የሰው ላብ ስናኝክበት!!! (ግጥም በሞገስ ሀብቱ፤ የጋዜጠኛው ማስታወሻ የተወሰደ) **** ከላይ ያለው ግጥም ግሩም ነው፡፡ ጥርሳችን ፈገግታን ፈልጎ አጣ ይለናል፡፡ ፈገግታም በሙሉ ልቡ የሚስቅበት ጥርስ ፈለገ፡፡ ግን የት ይምጣ፡፡ የሚስቁት ጥርስ የላቸውም፡፡ ጥርስ ያላቸው ደግሞ ማኘክን እንጅ መሳቅ የማይችል /የተሳነው ሆነባቸው፡፡ ከአካላቶቻችን ሁሉ የአዛዥነትን ሚና የሚጫወተው ሆድ ሆነ፡፡ ጥርስም ጌጥነቱን አቆመ፡፡ የሰው ላብ ያለበት የቆሸሸ ነገር ሲያኝክ እንደ በረዶ ጸዓዳ የነበረው ጥርስ ወየበ፡፡ ህሊናም ማሰቡን ትቶ ዙፋኑን ለሆድ ለቀቀ፡፡ ግብረ ገብነትም ከህሊና ጋ አብሮ ጠፋ፡፡ ህሊና ገልብጦ ማንበብ የጀመረለት ግብረ ገብነትም ይገለበጣል፡፡ ባለፈው ሳምንት ካቆምንበት ወሬ አልወጣሁም፡፡ ዛሬም ግብረገብነት ሆይ የት ነህ እያልኩ ነው፡፡ ግብረ ገብነትን በስም ሳይሆን በግብር ፍለጋ እየማሰንሁ ነው፡፡ በቤተሰብም በተቋምም፣ በግልና በቡድን፣ በተማረውና ባልተማረው፣ በሊቁም በደቂቁም፣ በአለቃውም በምንዝሩም፣ በገዢውም በተገዥውም በር ላንኳኳ ነው - ግብረ ገብነት ካለ በማለት፡፡ ድምጼን ከፍ አድረጌ ‹‹ግብረ ገብነት ሆይ ከቶ ከወዴት ነህ!›› እየተጣራሁ ነው፡፡ በየመስሪያ ቤቱ በር ደርዘን ያክል የሥነ ምግባር መርሆዎች ተጽፈው ባየሁበት ቢሮ አቅጣጫ ሁሉ አንኳኳው፡፡ ስማቸው ብቻ እንደ ሙት መታሰቢያ ሀውልት/ ፎቶ ተሰቅሎ አንድም እንኳ ማገኘት ተሳነኝ፡፡ እናም ዛሬ የ12ቱ ስነ ምግባር መርሆዎች አሉበት በተባለው ቦታ ሁሉ ዞሬ ያገኘገሁትን እና የደረስኩበትን የምርመራ ውጤት እንዲህ ሪፖርት ላቀርብ ወደድኩ፡፡ 1. የመንግስት የግዥ ሂደት፡ የግዥ የስራ መደብ ላይ ለመቀጠርና ለመስራት በጣም እድለኛ መሆንን ይጠይቃል፡፡ አሁን በቃ ግልጽ ነው፡፡ ግዥ የስራ መደብን በሀላፊነት ሳይሆን ባበለሙያነት መቀጠር ሎተሪ ከማሸነፍ የላቀ ነው፡፡ ግዥ የስራ መደብ ላይ የሚሰራ ሰው ወዳጁ ብዙ ነው፡፡ በዓመቱ እርሱም የመስሪያ ቤቱን ፍላጎት በማየት ራሱ አቅራቢ ድርጅት ይከፍታል - ይሉኝታ ያለበት በዘመዱ አሊያም በቤተሰቡ አይን ያወጣው ደግሞ በራሱ ስም፡፡ እቃ አቅራቢው ድርጅት ጋ መደራደር በጣም የተለመደ ነው፡፡ ግዥው በቀጥታ፣ በውስንና በግልጽ ጨረታ ሊካሄድ ይችላል፡፡ በቀጥታ ከሆነ ከምትፈልገው ባለሀብት ጋ ትሄዳለህ፡፡ ባለሀብችም ይጠይቃሉ - ‹‹ግዥው በመስሪያ ቤት ነው!›› የመስሪያ ቤት ዋጋ ከፍ ይላል፡፡ ትርፉ ከሁለት ይገመሳል፡፡ ‹‹ላምጪው እንዲከፈል ህግ ያስገድዳል›› ይላሉ የኮሚሽን ሲከፍሉ፡፡ ጀማሪ ገዥ ከሆነ በመጀመሪያው የሰጡትን ይቀበላል፡፡ ልምድ ያለው ባለሙያ ከሆነ ደግሞ ይከራከራል፡፡ ‹እንዴ ይኸ ለኔ ያንሳል፤ ወዳጅነታችንን ማሰብ አለብህ!›› ብሎ አቤቱታ ያቀርባል፡፡ ወይም ደግሞ መተሳሰብ ይጀምሩና የሂሳብ ሊቅ ሊቀጥሩም ይችላሉ፡፡ ባለሀብቱም የሚመጣውን ጊዜ በማሰብ ሳያቅማማ ይከፍላል፡፡ በተሻሻለው የመንግስት የግዥ ደንብ መሰረት አንድ መስሪያ ቤት እንደ ደረጃው ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ ግዥ በአንድ አመት በቀጥታ ግዥ ሊፈጽም ይችላል፡፡ በአንድ ጊዜ ደግሞ እስከ 50 ሺህ ብር ድረስ በአማካይ መግዛት እንደሚቻል መመሪያው ያዛል፡፡ በፕሮፎርማ ተሰብስቦ የሚገዛ ከሆነ ድግሞ አንዱን የምትግባባውን ባለሀብት ትመርጣለህ፡፡ ሶስት የዋጋ መሰብሰቢያ ቅጾችን ትሰጠውና ዋጋውን ሞልቶ በተለያየ ማህተም እና ንግድ ፈቃድ በፖስታ አሽጎ ይመልሳል - በለሀብቱ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ዋጋውን ራሱ የግዥ ባለሙያው ሞልቶ በፓስታ አሽጎ ማህተም ብቻ ለማስረገጥ ይሰጠዋል፡፡ ባለሀብቱ የተባለውን ያደርጋል - ግዢው በዚህ መልኩ ይፈጸማል፡፡ በግልጽ ጨረታ የሚካሄዱ ግዢዎች ትንሽ ወሰብሰብ ይላሉ፡፡ እርግጥ ነው ጠቀም ያለ ጉርሻ ያለውም ከዚሁ ግዥ ላይ ነው፡፡ አንዳንዴ ብዙ ሰዎችን ያነካካል፡፡ አሁን አሁን ተጫራቾችም አስቀድመው አለውህ ያላቸው ሰው ከሌለ በስተቀር የጨረታ ሰነድ አይገዙም፡፡ ቢገዙም ሰው ከሌላቸው እንደማያሸንፉ ያውቃሉ፡፡ ጨረታው የተከፈተ እለት የዋጋው ዝርዝር ታይቶ አሸናፊው በሌላ ቀን የሚነገርበት ጊዜ አለ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ድግሞ ጨረታው ሳይወጣ እንደወጣ ሆኖ አሸናፊው የሚነገርበትም ጊዜ አለ፡፡ እቃው ሳየይገዛ እንደተገዛ የሚሆንበት ጊዜም አለ፡፡ አላስፈላጊ ግዢዎችም ተገዝተው አገልግሎት ሳይሰጡ እቃዎቹ የሚበላሹበት ጊዜም አለ፡፡ በመስሪያ ቤቱ ሀላፊ ስምም የሚገዙበት አጋጣሚም አለ፡፡ እንዲያውም አንድ የክልል ባለስልጣን የነበረ በሀላፊነት ሲመራው በነበረው መስሪያ ቤት ውስጥ አንድ ቡልዶዘር በስሙ በእርዳታ ይሁን በግዥ በስሙ ገቢ ይሆናል፡፡ እናም ይህን ግለሰብ የክልል ቢሮ ሀላፊ መሆኑ አልበቃውም በማለት የሀይለ ማርያም መንግስት የሚኒስተርነት ማዕረግ እድገት ሰጠው ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ የአግልግሎት ዘመናቸው ያለፈባቸው እቃዎችም የሚገዙበት ጊዜ አለ፡፡ በተለይ መድሀኒት ከሆነ ደግሞ አደጋው የከፋ መሆኑ እየታወቀ የሚገዛው ሰው ምን አይነት አዕምሮ ቢኖረው ነው ያስብላል፡፡ በቃ ለሰው ልጅ ገንዘብ ብቻ ዘመዱ የሆነ ይመስላል፡፡ ለማንኛውም ከዚህ ቤት ግብረ ገብነትን አጣሁት፡፡ ግብረ ገብነት ሆይ የት ነህ! ሌላ 12 የስነ ምግባር መርህ የተጻፈበትን ታፔላ አየሁ፡፡ ከዚህ ቤትም ገባሁ፡፡ እንዲህም አገኘውት፡፡ 2. የህንጻ ጨረታዎችን በተመለከተ ብዙ ጊዜ ግንባታዎችን የሚያካሂዱ መስሪያ ቤቶች ገማች መሀንዲስ አካተው ኮሚቴ ያቋቁማሉ፡፡ ተቋራጩ ከመሀንዲሱ ግምት በአስር በመቶ ከፍ እና ዝቅ ብሎ ዋጋ በማቅረብ ሊያሸንፍ ይችላል፡፡ በጣም ዝቅ ካለ አቅም የለውም፤ በጣም ከፍ ካለ ደግሞ የተጋነነ በሚሉ ምክንያቶች ውድቅ ይሆናል፡፡ ገማች መሀንዲሱ የግንባታውን ዋጋ ለመገመት በመጀመሪያ ከሚፈልጋቸው ተጫራቾች ጋር ውሳኔ ያሳልፋል፡፡ በህንጻ ጨረታ ማፈን የምትባል ነገር አለች፡፡ የመሀንዲሱን ግምት ተቋራጩ አስቀድሞ እንዳወቀ ሁለት ወይንም ሶስት ጨረታዎች በተለያዩ ፈቃዶች በስም በታሸገ ኢንቬሎፕ ይቀርባል፡፡ አንደኛው የመሀንዲሱን ግምት የመጨረሻ ዋጋ የያዘ፣ ሁለተኛው ደግሞ የመሀንዲሱን ግምት ከፍተኛ ዋጋ የያዘ ሌላኛው ደግሞ መካከለኛ ይሆናል፡፡ ስለሆነም በመካከል ሌላ ተቋራጭ አለመግባቱ ከታወቀ ሁለቱ አሊያም አንዱ በፈቃዱ ከጨረታ ውጭ ይሆናል፡፡ በሲፒኦ ያሳዙት ገንዘብ ከሚገኘው ትርፍ ጋር ሲነጻጸር አናሳ ስለሚሆን ገንዘቡ ገቢ ይሆንና ጨረታው በከፍተኛው ዋጋ ይሆናል፡፡ በዚህ ብቻ አያበቃም፡፡ የህንጻው ጥራት እንዲሁ ይሆናል፡፡ ከልዩ ልዩ ነገሮች ላይ ማጭበርበር ይፈጠራል፡፡ የሲሚንቶውና የጠጠሩ ውህደት መጠን፣ የብረቱ ጥንካሬና ውፍረት፣ መስታዎቶቹ፣ ጅፕሰሙ፣ ቀለሙ… ሁሉም በተገኘው ክፍተት ሁሉ እንደነገሩ ይሆናሉ፡፡ በጣም ቀላል ወጭ የሚያስወጣውን ውሃ እንኳን በደንብ ማጠጣት አይታሰብም፡፡ ህንጻውም አንድ አመት ሳይቆይ አገልግሎት መስጠት ሊያቆም ይችላል፡፡ መንገድም ከሆነ አንድ አመት ሳያገለግል ይፈራርሳል፡፡ በቅርቡ እንኳ በአዲስ አበባ በአንደኛው ሆስፒታል ብዙ ሚሊዮን ብር ተከፍሎት የታደሰው ሆስፒታል አንድ ክረምት እንኳ ሳያገለግል መበላሸቱን በኢቲቪ አይናችን ፕግራም ስንመለከት የዚህን ቤት ግብረ ገብነት አሳሳቢ ያደረገዋል፡፡ አንድ እየተደጋገመ የሚወራ ነገር አለ፡፡ ነገሩ ቀልድ ቢመስልም እውነት ሳይሆን አይቀርም፡፡ ችግሩ የተፈጠረው ገነት ዘውዴ የትምህርት ሚኒስተርነቷን ልትለቅ አካባቢ ነው፡፡ በዪንቨርሲቲዎች የህንጻ ማስፈፊያ ጊዜ አንድ ክፍለ ሀገር ያለ ዩንቨርሲቲ ስድስት ህንጻዎችን አስገነባው ብሎ ሪፖርት ያቀርባል፡፡ በስራ ላይ ጉብኝት ጊዜ አንደኛው ጠፋ ተባለ፡፡ የዩንቨርሲቲው ባለስልጣናትም እንደማያውቁ አብረው ከእንግዶች ጋር ፍለጋ ያዙ፡፡ በመጨረሻ ቦሌ አካባቢ ቆሞ ተገኘ የሚል ቀልድ ይሁን እውነት ሰምቻለው፡፡ እንደ እውነታው ብዙ ባለሀብቶች ተቋራጭነትን የሚመርጡት የምህንድስና ባለሙያ ስለሆኑም፣ ትርፉም ጠቀም ያለ ስለሆነ ብቻ አይመስልም፡፡ ምክንያቱም ብዙዎቹ ተቋራጮች መሀንዲስ አይደሉም፡፡ ይልቁንም ከዚህ ቤት ብዙ ማጭበርበር ስለሚቻል እንጅ፡፡ በአጼው ዘመን የተሰሩ ህንጻዎች ለታሪክ ማህደርነት ወደፊትም ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ አሁን አሁን ግን የሚሰሩ ህንጻዎች የገንዘብ ፍቅርና አለመታመን ተጨማምረውበት ሁለት አስርት አመታትንም መድፈን አስቸጋሪ እየሆነ ነው፡፡ በተለይ በመንግስት የሚገነቡ ተቋማት ጉዳይ አሳሳቢ ነው፡፡ ጤና ጣቢያዎች፣ ትምህርት ቤቶች፣ ዩንቨርሲቲዎች፣ ቢሮዎች፣ አውራ መንገዶች … እነዚህ ሁሉ የጥራት ችግር ያለባቸው ናቸው፡፡ በዚህ ሰፈር ከአስራ ሁለት ምግባር አንድም ጠፋ፡፡ ታማኝነት፣ ቅንነት፣ የህዝብ አገልጋይነት…፡፡ አይገርምም!! ግብረ ገብነት ሆይ የት ነህ!! አሁንም ሌላ ‹‹ደንበኛ ንጉስ ነው›› የሚል ጽሁፍ የተሰቀለበት ቢሮ እያዘገምኩ ነው፡፡ በር አካባቢ ‹ግብርን በመክፈል የህዳሴ ጉዟችንን እናፋጥን› የሚል ባነር በር አካባቢ ያየሁበት ቤት ነው - ገቢዎችና ጉምሩክ፡፡ 3. ገቢ ግብር መጽሀፍ የቄሳርን ለቄሳር የእግዚአብሄርን ለእግዚአብሄር ይላል፡፡ በዚህም የሰራ ሁሉ እንደገቢው ግብር ይጣልበታል፡፡ መንግስት ሰራተኛው ከደመወዙ ላይ ይወሰዳል፡፡ ችግሩ ያለው ከነጋዴው ነው፡፡ ነጋዴ ልዩ ግብር ይጣልበታል - በመንግስት፡፡ በስራውም በሚያስወጣቸውና በሚያስገባቸው ሸቀጦችም እንዲሁ፡፡ አንደ ሰው ገቢዎችና ጉምሩክ ስራ ከገባ ‹የእንኳን ደስ አለህ› መልዕክት የሚመጣው ከብዙ አጃቢዎቹ ዘንድ ነው፡፡ በተለይ በሚገቡና በሚወጡ እቃዎች ላይ ያለው ማጭበርበር ቀላል እንዳልሆነ በአይንም የምናየው በሀሜትም የምንሰማው ነው፡፡ ከፍተኛ ባለስልጣኖቻችንም በዚህ ዓመት ቃሊቲ የወረዱት በዚሁ አይደል!! ገቢዎችና ጉምሩክ የሚሰሩ የነበሩ አሁን የናጠጡ ባለሀብች ሆነዋል፡፡ በክልል ገቢዎች የሚሰበሰቡ የስራ ግብር በቁርጥና በስሌት ለመጣል ሲታሰብ አሁንም ከላይ ካየናቸው የተለየ አይደለም፡፡ የግብር ግምት እና ክትትል ባለሙያዎቹ፣ የስራ ሂደት መሪው፣ ኦዲተሩ ሁሉም እነርሱ እንዳደረጉት ይሆናል፡፡ ባለሀብቱ ከባለስልጣኑ ጋር ከተስማማ በሚሊዮን የሚከፍለው ወደ ሽዎች ዝቅ ይደረግለታል፡፡ ባለሙያው በጎን በኩል የባለ ሀብቱ የግል ሂሳብ ሰራተኛ ይሆንና ከታክስ እንዴት ማምለጥ እንደሚችል ይሰራለታል፡፡ ይህን ያደረገው ባለሙያም ለስራው ይሸለማል፡፡ በቃ ሂዎት እንዲህ ነች፡፡ የገቢ ክትትል ባለሙያው የተሳሳቱ መረጃዎችን ለግብር ገማቹ ባለሙያ ያቀብላል፡፡ የግብር ገማቹ ባለሙያ ደግሞ ከገቢ ክትትል ባለሙያው የሚመጡትን መረጃዎች ያድበሰብሳቸዋል፡፡ ኦዲተሩ ከሁሉም የተዘለሉትን እርሱም ይዘላቸዋል፡፡ የስራ ሂደት በለሙያውና የቢሮው ሀላፊ ደግሞ ከፍተኛ ግብር ከፋዮችን ይከታተልና እንደሚሆን ያደርጋል፡፡ በጣም የሚያሳዝነው ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውና በችርቻሮ የሚተዳደሩ ሰዎች የንግድ ድርጅት በጥቃቅን ስህተት ሊታሸግ ሲችል ከፍተኛ ገቢና ትልቅ ድርጅት ያላቸውን ሰዎች ግን ከጥቃቅን ባለሀብቶች ላይ እንደፈለገ የማድግ ስልጣን የነበረው ባለሙያው የመናገር ስልጣን የለውም፡፡ ገንዘብ አሊያም ባለስልጣን ዘመድ ያለው በለሀብት የፈለገውን ያደርጋል፡፡ ቫት ሊያጭበረብር፣ ገቢው ሊደብቅ ይችላል፡፡ ፍርድ ቤት ሌባ እስካላለህ ድረስ በየትም የተገኘ ገንዘብ ይሁን ሀብትህ ነው፡፡ ባለሀብቱም፣ ባለሙያም፣ ባለስልጣኑም ተባብረው ለመንግስት ገቢ የሚሆነው ገንዘብ ይወስዱታል፡፡ መንግሰት መንግስትን ይሰርቃል፤ ህዝብ ህዝብን ይሸውዳል፡፡ የዚህ ቤት ገብረ ገብነት ይህ ነው፡፡ የተባለውን ላለመክፈል ያቅማማ ባለሀብት አገር ካልቀየረ በስተቀር መስራት አይችልም፡፡ ውሃ በቀጠነ ማስፈራሪያ ይደርሰዋል፡፡ እርግጥ ነው የተሰበሰበውም ገንዘብ አግባብ ላይ ይውላል ማለት አይቻልም፡፡ ግን በየቦታው ይመዘበራል፡፡ ታዋቂው የስነ ጽሁፍ ሰው ሸክስፒር እንዲህ አለ፡ ምናልባት ገንዘብ እድሜን አያራዝም ይሆናል፣ አሊያም እርሱ ያልደረሰበት ፍልስፍና ነው፡፡ ሸክስፒርም ይቀጥል፡ Life is cycle which turns on the wheel Starts on the womb ends on the tomb If life is a thing which money would buy The rich will live and the poor will die But nature in its wisdom made it too The rich and the poor together must go!! አይ እግዚአብሄር ደጉ ሀብታምንም ደሀንም አንድ ማድረጉ በጀን፡፡ እንጅማ!! ሰው የገንዘብ ባሪያ ሆነ ማለት ይህ ነው፡፡ በየትኛውም በኩል ይምጣ ብቻ ገንዘብ ይሁን፡፡ የሰው ህይወትም ለውጥ ይሁን፡፡ አዎ ገንዘብ ገንዘብ ገንዘብ፡፡ የዚህ ትውልድ አደገኛ አካሄድ ፍቅረ ንዋይ ነው፡፡ ግብረ ገብነት ከዚህ ቤት አጣሁት አሁን ፍለጋውን እቀጥላለሁ፡፡ አንድ ቀን አንድ ቦታ ላገኘው እችላለሁ ብየ ተስፋ በማድረግ፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት ሌላ ቤት አንኳኳለው፡፡ እስከዚያው መልካም ሳምንት!! ይቀጥላል!! ሰላም

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ