2014 ማርች 13, ሐሙስ

በሸንቁጥ አየለ የተደረሰዉ ኅቡእ ጣት (ዘ ሀይድ) መጽሀፍ ዕሁድ መጋቢት 7/2006 ዓም በሀገር ፍቅር ቲያትር ይመረቃል በሸንቁጥ አየለ የተደረሰዉ ኅቡእ ጣት (ዘ ሀይድ) መጽሀፍ ዕሁድ መጋቢት 7/2006 ዓም በሀገር ፍቅር ቲያትር ከጠዋቱ 3 ሰዓት እስከ 6 ሰዓት ይመረቃል:: በምርቃት ፕሮግራሙ ላይ ታዋቂ ሰዎች : ጋዜጠኞችና የስነ ጽሁፍ ባለሞያዎች ተገኝተዉ ስለ መጽሃፉ ያላቸዉን አስተያዬት ይሰጣሉ:: ኅቡእ ጣት (ዘ ሀይድ) መጽሀፍ ኢትዮጵያ በዉስጡዋና በዙሪያዋ ባሉ ልዩ ልዩ ስነልቦናዊ: ታሪካዊ : ፖለቲካዊ: ሳይንሳዊና ማህበራዊ ጭብጦች ዙሪያ የሚያጠነጥን መሆኑ ተገልጾአል:: ዙሪያዋን ያሉ ታላላቅ የሀገሪቱ ጠላቶች ኢትዮጵያ ፈርሳ ማዬት ትልቁ የቤት ስራቸዉ ብቻ ሳይሆን ከፍ ያለ ቅዱስ ተልዕኮአቸዉም መሆኑን የሚተርከዉ ይህ መጽሀፍ የሚያጠነጥነዉ የሀገሪቱ ባላንጣዎች ታላቁን የቤት ስራቸዉን ብሎም ቅዱስ ተልዕኮአቸዉን ለማሳካት በታላቅ ትጋት : በከፍተኛ ጥበብና በሙሉ ሀይላቸዉ ስራቸዉን ሲከዉኑ ያሳያል ተብሎአል:: ሀገሩ ያበሳቆለችዉንና የገፋችዉን ተራ ዜጎች ብሎም መንግስት ጆሮ አልስጥ ያላቸዉን ታታላቅ ሳይንቲስቶችን ጭምር ለዚህ ተልዕኮ ሊያሰልፉዋቸዉ ሲባትቱ የሚከተሉዋቸዉን ሂደቶች ልብ ሰቃይ በሆነ መልክ ያሳያል:: ይህ መጽሀፍ ሳይንስ በኢትዮጵያ ምድር ፍሬ እንዲያፈራ ከተፈለገ ባለ አዕምሮ የሀገሪቱ ዜጎች የሚሉትን በጥንቃቄ ማድመጥ ወሳኝ መሆኑን ለማሳዬት እንደሚሞክር ተገልጾአል:: የሀገሪቱ ብሄሮች ወደ ከፍተኛ ቅራኔና የእርስ በእርስ መጠፋፋት እንዲገቡ በመጨረሻም ሀገሪቱ ፍርስርሱዋ እንዲወጣ ሁሉንም አሉታዊ ድሮች የሚያደሩት የሀገሪቱ ባላንጣዎች ብርና ሀብታቸዉን በኢትዮጵያ ምድር እንደ ጉድ ሲያፈሱት የሚያሳይ ብሎም ስለላ : ንግድ እና ሸፍጥ ተጎናጉነዉ ሲጦፉ የሚተርክ መጽሀፍ መሆኑን ደራሲ ሸንቁጥ አየለ አብራርቶአል:: ሀገር ከሰራዊት በላይም የዜጎቹዋ ጥበቃ የግድ ያስፈልጋታል በሚል ጽኑ መርህ ላይ የቆመ መልዕክት ያለዉ ይህ መጽሀፍ የግብጽና የሌሎች ጎረቤት ሀገራት ኢትዮጵያን የማፍረስ ተልዕኮ በኢትዮጵያዉያን ዜጎች እንዲከሽፍ ከተፈለገ ከብሄረተኝነት ይልቅ ኢትዮጵያዊነት ብቸኛ መሳሪያ ነዉ የሚል ጥልቅ ይዘትን እንደሚያስተላልፍ ታዉቁአል:: በአጠቃላይ ኢትዮጵያ ባላት የዉሃ ሀብትና ሌሎችም ተያያዥ ሀብቶች ግብጽ ስታገሳ ኤርትራ ስትወናጨፍ ሌሎች ጠላቶች እያጨበጭቡ ኢትዮጵያ ያላትን ሁሉ ሊያሳጡዋት ቢዘጋጁም ኮሳሶቹ ኢትዮጵያዊ ዜጎች ግን ኢትዮያዊነትን እንደ ኒኩሊየር አረር ሲተፉ የሚተርክ መጽሀፍ መሆኑ ታዉቆአል:: 206 ገጽ ያለዉ ኅቡእ ጣት (ዘ ሀይድ) መጽሀፍ የሸንቁጥ አየለ ሁለተኛ የመጽሀፍ ስራዉ ሲሆን ከዚህ በፊት የጠፍ ከዋክብት የሚል መጽሀፍ ማሳተሙም ታዉቁዋል:: ደራሲዉ ከዚህ በተጫማሪም ማዕበል የሚል ፊልም ደርሶ ለህዝብ ማቅረቡና ልዩ ልዩ ጽሁፎችን በተለያዩ ሚዲያዎች ላይ ለአንባቢያን የሚያቀርብ መሆኑ ተገልጾአል:: ኅቡእ ጣት (ዘ ሀይድ) መጽሀፍ ከመጋቢት 7/2006 ዓም ጀምሮ በገበያ ላይ እንደሚዉል ደራሲዉ ገልጾአል::

1 አስተያየት:

  1. አንተን ወንድሜንና ሸንቁትን የመሳሰላችሁ ኢትዮጵያዉያን ጸሃፊወች ብቅብቅ ማለት ለዘመናት እንዲጎብጥ የተደረገዉን የመረጃ አቅርቦት የሚያርቅ ከመሆኑም በላይ በአማርኛ የስነ ጽሁፍ እድገት ላይም ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደርጋል። በርቱ። ለሌሎች ወጣት ደራሲያንም ምሳሌ ሁኑ።

    ምላሽ ይስጡሰርዝ