2014 ማርች 24, ሰኞ

አማላጅ ያልተገኘለት የኢትዮ ቴሌ ኮም ጉዳይ - Disconnecting the Future


ስሙን እና አርማውን ብቻ ቀይሮ በግብር ግን ወደ ኋላ እየተንቀሳቀሰ ያለ ተቋም እንደ ኢትዮቴሌኮም አይገኝም፡፡ አንድ ጊዜ የፈረንሳይ ሌላ ጊዜ ደግሞ የቻይና ኩባንያወዎች እየተፈራረቁበት የሚገኘው ኢትዮቴሌኮም አሁን አሁን በተለይም ከቅርብ ወራት ጀምሮ አገልግሎት እየሰጠ ነው ማለት የሚከብድ ይመስለኛል (ምናልባትም ከስለላ ስራው ውጭ)፡፡ በአፍሪካ አነስተኛ ደንበኞችን በብቸኝነት ይዞ ጥራት ያለው አገልግሎት መስጠት የተሳነው አንጋፋው ድርጅት ነው፡፡ በእድሜ ብዛት ለውጥ አቅቶታል፡፡ ጎረቤት አገራት በርካታ የቴሌ ኩባንያዎች አላቸው፡፡ ሱዳን ውስጥ ከአራት በላይ አገልግሎቱን የሚሰጡ ተቋማት አሉ፡፡ ሱዳኒ፣ አረቢ፣ ኤም ቲ ኤን ... ይጠቀሳሉ፡፡ በጸጥታው ዘርፍ እንኳ እየታመሰች ያለችው ጎረቤት ሀገር ሶማሊያ ሶምቴል፣ ቴሌሶም፣ ቴሌኮም፣ ኤም ቲ ኤን የሚባሉ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት አሏቸው፡፡ ከኬንያ ጋር መወዳደር አይቻልም፡፡ ታዲያ ምንም አማራጭ በሌለበት ሁኔታ ይህ ተቋም ከዘመድ አዝማድ ሁሉ ሊያቆራርጠን ነው፡፡ ከሚያውቁት ሰው ሲደውሉ የማያውቁት ሰው ያነሰዋል፡፡ ይቅርታ ጠይቀው እንደገና ያንኑ ቁጥር ሲመቱት በመካከል ሙዚቃ ይገባብዎታል፡፡ ሙዚቃው እስኪጨርስ ከጠበቁት በራሱ ጊዜ ይዘገዋል፡፡ አሁንም ሌላ ዘመድዎ ጋር ቢደውሉ ጆሮ የሚያደነቁር ድምጽ ሊሰሙ ይችላሉ፡፡ ሌላ ሰው ጋ ሳይሰለቹ ከደወሉ ከብዙ ሙከራ በኋላ ‹‹ይቅርታ የደወሉለትን ደንበኛ አሁን ማግኘት አይችሉም›› የሚል ሰቅጣጭ ድምጽ ይሰማሉ፡፡ የዚች ሴቲዮ ድምጽ በስልክዎ ሲያሰለችዎት ስልክዎን ሊወረዉሩ ይችላሉ፡፡ በዚህ መካከል ሁለት ነገሮች ያልቃሉ፡፡ አንደኛው ገንዘብዎት ምንም ሳያወሩ ያልቃል፡፡ ሁለተኛው የሞባይሉ ባትሪ እንዲሁ ያልቃል፡፡ የኢትዮጵያ መብራት ሀይል እርሱም መብራቱን አጥፍቶት ከሆነ ለቀናት የተዘጋ ሞባይል ቀፎ ይዞ ለመዞር እንገደዳለን፡፡ እናም በዚህ አካሄድ በ2020 ኢትዮጵያውያንን ከዓለም ጋር ብቻ ሳይሆን ከኢትዮጵያውያን ጋር የሚቆራርጠን ይሆናል፡፡ አይበልብንና ሌባ ቢመጣ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ከመደወል ሰወው መላክ ይቀላል፡፡ ስልክ እስኪደወል ወንበዴው የፈለገውን ማድረግ ይችላል፡፡ አማልዱን ብለን አማለጅ አንልክ በማን እንሂድበት!! የጃን ሆይን ሞዓ አንበሳ አርማ አስወግዶ ኔትወርኩንም ኖት ዎርክ (Network to Not-work) አደረጎት አረፈ፡፡ እንደባለፉት ዘመናት ሁሉ በፖስታ በኩል መላላክ ብቸኛው አማራጭ ሊሆን ነው፡፡ የፖስታ ቤት ባለስልጣን ማርኬቲንግ ክፍል አስቦበት ከሆነ በርከት ያሉ የፖስታ ቁጥሮችን እንዲሁም ቅርንጫፎቹን ማብዛት ያለበት ይመስለኛል፡፡ ቴሌኮም እንደሆን ከቀን ቀን እየሆነ ያለውን እያየነው ነው፡፡

1 አስተያየት:

  1. This is also my feeling,Please give attention ethiotelecom.The difficult Sector in Ethiopia 1)thiotelecom
    2)Electricity
    3)Water supply because of Monopoly market system.

    ምላሽ ይስጡሰርዝ